በመጀመሪያው ግማሽ በጀት ዓመት ከ377 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉ ተገለጸ፡፡
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ 6 ወራት ከ377 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ያስመዘገቡ 64 ባለሃብቶች ኮርፖሬሽኑ በሚያስተዳድራቸው ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖችና ኢንዱስትሪ ፓርኮች መሳብ መቻሉ ተገልጿል፡፡
ኮርፖሬሽኑ የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ 6 ወራት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት በአዳማ ክተማ በመገምገም ላይ ይገኛል፡፡
ወደ ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖች ገብተው ሀብት እና እውቀታቸውን ስራ ላይ ላማዋል የወሰኑ ባለሃብቶች በንግድና ሎጅስቲክስ፤በፋርማሲዩቲካል፤አግሮ ፐሮሰሲንግ ፤ኢንጅነሪንግና ብረታ ብረት ፤ኮንስትራክሽንና ፈርኒቸር እንዲሁም አልባሳትና ጨርቃ ጨርቅ የተሰማሩባቸው ዘርፎች መሆናቸውን በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
ባለሃብቶቹ የተሰማሩበት የስራ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን ኢንቨስትመንቱ የተሳበበት ሃገር ብዝሃነት እንዳለው በሪፖርቱ የተጠቆመ ሲሆን የቻይና ፤ የአሜሪካ፤የእንግሊዝ ፤የህንድ እና የጅቡቲ ባለሃብቶች እንደሚገኙበት ተገልጿል ።
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በሚያስተዳድራቸው ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖችና ኢንዱስትሪ ፓርኮች ገብተው በመስራት ላይ በሚገኙ ባለሃብቶች ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች ከ112.6 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱ ይታወሳል፡፡