ያልተያዙ የማምረቻ ሼዶችን ለማስያዝ የተከናወኑ አበረታች ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተገለፀ
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኢኮኖሚ ዘርፍና የመንግስት የልማት ድርጅቶችን የሚከታተል ቋሚ ኮሚቴ የቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ ወቅታዊ የስራ እንቅስቃሴና አፈፃፀም ተመልክቷል።
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አክሊሉ ታደሰ ኮርፖሬሽኑ እንዲሁም ስለሁሉም ኢንዱስትሪ ፓርኮች እና ስለ ድሬዳዋ ነፃ ንግድ ቀጠና ወቅታዊ እንቅስቃሴ ገለፃና ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ዋና ስራ አስፈፃሚው ከስራ እድል ፈጠራ፤ ከወጪ ቅነሳ፤ ከገቢ፤ ተኪ ምርት ከማምረትና ከውጪ ምንዛሪ፤ ከትርፍና ከማምረቻ ሼዶች የመያዝ ምጣኔ ጋር አያይዘው ያሉ አፈፃፀሞችን ለቋሚ ኮሚቴው አብራርተዋል።
ቋሚ ኮሚቴው በቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ የሚገኙ ሺንትዝ እና ጄጄ የተሰኙ ሁለት ኩባንያዎችን ተዟዙረው ተመልክተዋል። ከምልከታው ባሻገር በተደረገ ውይይትም በኢንዱስትሪ ፓርኮች ለሰራተኞች የሚገነቡ ቤቶች፤ የህፃናት ማቆያ ስፍራዎች እና የስራ እድል ፈጠራ ላይ ያሉ አፈፃፀሞች አበረታች መሆናቸውን ቋሚ ኮሚቴው አሳውቋል።
ቋሚ ኮሚቴው ከዚህ ቀደም ሌሎች ኢንዱስትሪ ፓርኮችን የተመለከተ ሲሆን ኮርፖሬሽኑ ትርፋማነቱን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባውና ያልተያዙ የማምረቻ ሼዶችን ለማስያዝ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች መጠናከር እንደሚገባቸው ጠቁሟል።