ከ6 ቢሊየን ብር በላይ ሀብት ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ስራ ለመጀመር የልዩ ኢኮኖሚ ዞን አዋጅ መጽደቅን በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ ተገለፀ
ይህንን የገለፁት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አክሊሉ ታደሰ ኮርፖሬሽኑ ባዘጋጀው የድሬዳዋ ነፃ የንግድ ቀጠና የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ ላይ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ነው።
ዋና ስራ አስፈፃሚው እንደገለፁት በነጻ ንግድ ቀጠናው እስካሁን ከተደረጉ በቢሊየን ብሮች ከሚገመት የሞዋለ ነዋይ ፍሰት በተጨማሪ ከ6 ቢሊየን ብር በላይ ሀብት ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ከኮርፖሬሽኑ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመው ስራ ለመጀመር የሚያስችላቸውን የልዩ ኢኮኖሚ ዞን አዋጅ መጽደቅ በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ አዋጁ ባለፈው ሳምንት በሚኒስትሮች ምክር ቤት ጸድቆ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መመራቱ ይህንን ተስፋ የበለጠ እንደሚያለመልመው ኮርፖሬሽናቸው እንደሚያምንም አቶ አክሊሉ አክለዋል፡፡
ኮርፖሬሽኑም የድሬዳዋ ነጻ ንግድ ቀጠና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ለደንበኞቹ መስጠት የሚያስችሉ መሰረተ ልማቶችን ማሟላቱንና አስቻይ የአሰራር ስርዓትና የባለሀብት መመልመያ መስፈርት እንዲሁም የአገልግሎት ዋጋ ተመን መዘጋጀቱን ጨምረው አሳውቀዋል።
በዚህም የተለያዪ ባለሙያዎች እና ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ አድርገዋል ያሉት ዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ አክሊሉ የጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤት፤ ገንዘብ ሚንስቴር፤ ብሔራዊ ባንክ፤ የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክ ድርጅት፤ የኢንቨስትመንት ኮምሽን፤ የጉምሩክ ኮምሽን፤ የፌደራል ፖሊስ፤ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፤ የመንገዶች ባለስልጣን ተጠቃሽ መሆናቸውን ጠቁመው ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
አያይዘውም የድሬዳዋ ነጻ የንግድ ቀጠና ውጤታማ እንዲሆን ለማስቻል በማሰብ የተለያዪ ሀገራት በነጻ ንግድ ቀጠና አስተዳደር ዙሪያ ያላቸው ተሞክሮ እና ልምድ በኮርፖሬሽኑ መቀመሩን አውስተው በዚህ ረገድ የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች፣ የቱርክ እና የጅቡቲ ተሞክሮ በስፋት እና በጥልቀት ተዳሶ የድሬዳዋ የነጻ የንግድ ቀጣና ባለንበት ስነ ምድራዊ ፖለቲካ ውስጥ ተወዳዳሪ እና ተመራጭ እንዲሆን ያስችላል ተብሎ የታመነባቸው አሰራሮች ተቀርጸው ተግባራዊ እንዲሆኑ ተደርጓል ብለዋል።